ማህበሩ ከኢትዮ ቴሌኮም የተደረገለትን የአምቡላንስ ድጋፍ ተረከበ
February 12, 2019
ኢትዮ ቴሌኮም 980 ሺህ ብር የሚያወጣ የአምቡላንስ ድጋፍ ለኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማህበር አበረከተ፡፡ ድርጅቱ ሠራተኞቹን በማስተባበር አሁን ያበረከተውን አምቡላንስ ጨምሮ በተለያዩ ሰብዓዊ ተግባራት ድጋፍ ለመስጠት ከማህበሩ ጋር በትብብር እንደሚሰራ አስታውቋል፡፡
የካቲት 04 ቀን 2011 ዓ.ም በማህበሩ አዲስ አበባ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት በተካሄደው ርክክብ ስነ ስርዓት ላይ የተገኙት አዲሱ የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማህበር ዋና ፀሀፊ ዶ/ር መሸሻ ሸዋረጋ፣ ኢትዮ ቴሌኮም ላደረገው ድጋፍ ያላቸውን ምስጋና ገልፀው ሌሎች ተቋማትም ይህንን አርአያ እንዲከተሉ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት በሀገራችን ከ10 ሚሊዮን በላይ ሰብዓዊ ዕርዳታ ፈላጊ ወገኖች መኖራቸውንና እነዚህን ተደራሽ ለማድረግ ለስድስት ወር ብቻ 1.5 ቢሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልግ የተናገሩት ዶ/ር መሸሻ፣ በዚህ ረገድ ያለውን ክፍተት ለመሙላት የማህበሩ የበላይ ጠባቂና የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፕሬዚዳንት አስተባባሪነት የሚመራ ኮሚቴ በማቋቋም ለሰብዓዊ እርዳታ የሚውል ገንዘብ ለማሰባሰብ በዝግጅት ላይ እንገኛለን ብለዋል፡፡
የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈፃሚ ወ/ት ፍሬህይወት ታምሩ በበኩላቸው፣ ሰብዓዊነት ትልቅ ተግባርና ኃላፊነት በመሆኑ የዚህ ዓላማ አጋር በመሆናችን ደስታ ይሰማናል ብለዋል፡፡ የተቋሙ ሠራተኞችም በየወሩ ከደሞዛቸው ከሚያደርጉት የአባልነት መዋጮ ባሻገር በበጎ ፈቃደኝነት በዓመት ሁለቴ የደም ልገሳ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል፡፡ በሀገራችን ያለውን የሰብዓዊ እርዳታ ፍላጎት ማቃለል የምንችለው ስንተባበር በመሆኑ ተቋማት ማህበራዊ ኃላፊነታቸውን ሊወጡ ይገባል ያሉት ወ/ት ፍሬህይወት ተቋማቸው ከማህበሩ ጋር ተባብሮ በመስራት በቀጣይም መሰል ድጋፎችን ማድረግ እንደሚቀጥል ገልፀዋል፡፡
የማህበሩ የአዲስ አበባ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ቦርድ አባልና የረጅም ዓመታት የቀይ መስቀል ቤተሰብ የሆኑት አርቲስት ፋንቱ ማንዶዬ፣ የኪነ ጥበብ ባለሞያዎች በሰብዓዊ ተግባር ላይ በመሰማራት የበኩላቸውን ኃላፊነት እንዲወጡ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡
ኢትዮ ቴሌኮም ከ20 ዓመት በፊት በ1000 ብር የድርጅት አባልነት መዋጮ ጀምሮ በየዓመቱ በማሳደግ ከ2008 ዓ.ም ጀምሮ በዓመት ለማህበሩ 100 ሺ ብር ድጋፍ የሚያደርግ ሲሆን ከ15000 በላይ ሰራተኞቹ ደግሞ የቀይ መስቀል መደበኛ አባል በመሆን በወር ከ30 ሺ ብር በላይ ድጋፍ ያደርጋሉ፡፡ በተጨማሪም የተቋሙ ሠራተኞች ማህበር እንደተቋም አባል በመሆን በየዓመቱ የ50 ሺህ ብር ድጋፍ ያደርጋል፡፡
የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማህበር ከሚሰጣቸው ሰብዓዊ አገልግሎቶች መካከል ነፃ የ24 ሰዓት የአምቡላንስ አገልግሎት አንዱ ሲሆን በዓመት በአማካኝ በአንድ አምቡላንስ ለ3600 ሰዎች አገልግሎት ይሰጣል፡፡