እናቶች በኢቀመማ በኩል ለተፈናቃዮች መርጃ የሚሆን የ150,000 ብር ድጋፍ አደረጉ
April 17, 2019
የቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 08 እናቶች “የተጎዳን ለመርዳት እናት መሆን በቂ ነው” በሚል መሪ ቃል ለተፈናቃይ ወገኖች መርጃ የሚሆን 150,000 ብር እና የተለያዩ አልባሳትን በማሰባሰብ ለኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር ሚያዝያ 05 ቀን 2011 ዓ.ም አበርክተዋል፡፡ ድጋፉን የእርዳታ አሰባሳቢ ኮሚቴው ሰብሳቢ ወ/ሮ ሶሪት ከሊፋ ለማኅበሩ ቦርድ አባል አምባሳደር ዶ/ር ቶፊቅ አብዱላሂ አስረክበዋል፡፡
በስነ-ስርዓቱ ላይ የድጋፍ አሰባሳቢ ኮሚቴ አባል የሆኑት ወ/ሮ ሀመረ ታደገ እንደተናገሩት፣ ይህ በጥቂት እናቶች የተጀመረውን እንቅስቃሴ በማስፋትና የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮጀክቶችን በመቅረፅ እንዲሁም ባለሀብቶችና ድርጅቶች ተሳታፊ እንዲሆኑ ጥሪ በማድረግ በቀጣይ እንቅስቃሴ የሚደረግ ይሆናል፡፡
“እናቶቹ የበጎ አድራጎት ሥራውን ለማከናወን ሶስት ዓመታትን የሚሸፍን ራዕይ ቀርፀው ወደ ተግባር ለመግባት የቅድመ ዝግጅት ተግባራትን እያከናወኑ ነው” ያሉት ወ/ሮ ሀመረ፣ “የዛሬዋ ዕለትም ቀጣይ እቅዳችንን የምናሳውቅበት፣ ለወጣት ልጆቻችን የእናትነት የሰላም ጥሪ የምናስተላልፍበት እንዲሁም በአደጋ ምክንያት ደም ለሚያሻቸው ወገኖቻችን የደም ልገሳ የምናደርግበት ነው” ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር የቦርድ አባል አምባሳደር ዶ/ር ቶፊቅ አብዱላሂ በበኩላቸው፣ የወረዳው እናቶች ያከናወኑት ተግባር ሌሎች እናቶችንም የሚያነሳሳና ትልቅ አርዓያ መሆኑን ተናግረው፣ “የሰበሰባችሁት እርዳታ ለተፈናቃይ ወገኖች በኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር በኩል እንዲደርስላችሁ ስላደረጋችሁ ኮርተንባችኋል” ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር በተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋ ለተጋለጡ ወገኖች የሚሰጠውን ሰብዓዊ አገልግሎት በይበልጥ ለማስፋት የበጎ ፈቃደኞቹ ሚና ከፍተኛ በመሆኑ የአካባቢው ማኅበረሰብ የማህበሩ በጎ ፈቃደኛና አባል በመሆን ድጋፍ እንዲያደርግ አምባሳደር ዶ/ር ቶፊቅ ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡
በተደረገው ገንዘብ ማሰባሰብ ላይ 170 የሚሆኑ እናቶች መዋጮ በማድረግ የተሳተፉ ሲሆን በዕለቱ የአካባቢው ነዋሪዎች የደም ልገሳ አድርገዋል፡፡